በኢትዮጵያ እና ኤርትራ ድንበር ላይ የነበረው የድንጋይ አጥር ፈረሰ

የፎቶው ባለመብት, Mulu Birhan
የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ሠራዊት አባላት
ከዛላምበሳ ወደ ሰንዓፈ የሚወስደውን መንገድ ዘግቶ የቆየው የድንጋይ አጥር ዛሬ ፈርሷል።
የኢትዮጵያዋ ዛላምበሳ እና የኤርትራዋ ሰንዓፈ መካከል የነበረው የድንጋይ ግንብ እንዲፈርስ ተደርጓል።
በአካባቢው የነበሩ የዓይን እማኞች እንደሚሉት ከሆነ ከዚህ በተጨማሪ በአካባቢው የነበረው የኤርትራ ጦር ምሽግም እንዲፈርስ ተደርጓል።
የሁለቱም ሀገራት የሰራዊት አባላት በጋራ የፈንጂ ማፅዳት ስራ ማከናወናቸውንም የዓይን እማኞቹ ተናግረዋል።
የፎቶው ባለመብት, Mulu Birhan
"ከኤርትራ በኩል ምሽጉን ማፍረስ የጀመሩት ማለዳ 12 ሰዓት ነው። ወታደሮች ናቸው ያፈረሱት። ከኢትዮጵያ በኩል ደግሞ መንገዱን ዘግቶት የነበረው የደንጋይ አጥር በህዝቡና ሠራዊቱ እንዲፈርስ ተደርጓል" ሲል በቦታው ተገኝቶ ክስተቱን የተከታተለው ዮናስ ፍሰሃ ለቢቢሲ ተናግሯል።
የድንበሩን መከፈት በማስመልከት ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት በተገኙበት ነገ በቦታው ይፋዊ ሥነ-ስርዓት ይካሄዳል።