ፕሪሚየር ሊግ ፡ የላውሮ የሳምንቱ ጨዋታዎች ግምት

የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
በጥሩ አቋም ላይ የሚገኘው ቶተንሃም እና አዳዲስ ተጫዋቾችን ያስፈረመው አርሴናል ቅዳሜ በለንደን ደርቢ ይገናኛሉ። ቶተንሃም በኤምሬትስ የደረሰበትን ሽንፈት ይበቀል ይሆን?
የቢቢሲው እግር ኳስ ተንታኝ ማርክ ላውረንሰን "ቶተንሃሞች ከተሸነፉ ቆዩ። ይህም በምርጥ አቋም ላይ መሆናቸውን ያሳያል" ይላል።
"አርሴናሎች ደግሞ ዘንድሮ ከሜዳቸው ውጭ ካደረጓቸው 13 ጨዋታዎች ሶስቱን ብቻ ነው ማሸነፍ የቻሉት። ይህ ችግር በዌምብሌይም እንደሚከተላቸው አስባለሁ" ብሏል።
የሳምንቱን የላውሮ የፕሪሚየር ሊግ ግምቶች እንደሚከተለው አቅርበንላችኋል።
ቅዳሜ
ቶተንሃም ከአርሴናል
አርሴናሎች ፒር-ኤመሪክ አውባሜያንግ እና ሄነሪክ ሚኪታሪያንን በማስፈረም የአጥቂ መስመራቸውን ቢያጠነክሩም ተመሳሳይ ስራ በተከላካይ መስመራቸው ላይ አልሰሩም።
የቶተንሃሞችን ተከላካይ መስመር ማለፍ ከባድ ሲሆን የአጥቂ መስመራቸውም ጨዋታዎችን ማሸነፍ ይችላል።
የላውሮ ግምት፡ 2-0
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ኤቨርተን ከክሪስታል ፓላስ
ኤቨርተኖች ባለፈው ከአርሴናል ጋር በነበራቸው ጨዋታ ይዘውት የገቡት የታክቲክ ስህተት ነበር። ክሪስታል ፓላሶች ደግሞ ከኒውካስትል ጋር አቻ ቢለያዩም ማሸነፍ የሚችሉባቸው ብዙ ዕድሎችን አልተጠቀሙበትም።
ፓላሶች ከወራጅ ቀጠና በሶስት ነጥብ ብቻ ርቀው ስለሚገኙ ሊጠነቀቁ ይገባል። ሶስት ወይም አራት ጨዋታዎችን ሳያሸንፉ ከቀሩ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገባሉ።
የላውሮ ግምት፡ 2-1
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ስቶክ ከብራይተን
ብራይተኖች ባለፈው ሳምንት ዌስት ሃምን በማሸነፍ ወደ 13ኛ ደረጃ ከፍ ብለዋል። ከወራጅ ቀጠናውም በሶስት ነጥብ ርቀዋል።
ባለፈው ሳምንት ስቶኮች 1 ለ 0 ከመምራት በበርማውዝ ተሸንፈዋል።
የላውሮ ግምት፡ 1-1
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ስዋንሲ ከበርንሌይ
ስዋንሲዎች በአዲሱ አሰልጣናቸው ካርሎስ ካርቭሃል ስር በመሻሻል ላይ ይገኛሉ። ካለፉት አምስት ጨዋታዎችም 10 ነጥቦችን አግኝተዋል።
በርንሌይዎች ካሸነፉ ረዥም ጊዜ ቢሆናቸውም ይህ ግን በቅርቡ ይቀየራል ብዬ አስባለሁ።
የላውሮ ግምት፡ 0-2
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ዌስት ሃም ከዋትፎርድ
ማንም ባልጠበቀው መልኩ ዋትፎርዶች ባለፈው ሰኞ ቼልሲን በማሸነፍ ትልቅ ውጤት አስመዝግበዋል።
ዌስትሃሞች ጉዳት ላይ የነበረው ማርኮ አርናቶቪች የሚመለስ እና አዲስ ያስፈረሙት ፓትሪስ ኤቭራም የሚሰለፍ ቢሆንም ችግር ውስጥ ይገኛሉ።
የላውሮ ግምት፡ 1-0
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ማንቸስተር ሲቲ ከሌስተር
የሌስተሩ ሪያድ ማህሬዝ በተጠናቀቀው የዝውውር መስኮት ሊያቀና ከነበረበት ክለብ ጋር የማይሰለፍ ይሆናል።
ማንቸስተር ሲቲዎች ባለፈው ሳምንት ከበርንሌይ ጋር በነበራቸው ጨዋታ ሁለት ነጥብ ቢጥሉም አሁን ግን ወደ ለመዱት መንገድ ይመለሳሉ።
የላውሮ ግምት፡ 2-0
እሁድ
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ሃደርስፊልድ ከበርንማውዝ
ሃደርስፊልዶች ወደ 5ኛው ዙር የኤፍ ኤ ካፕ ውድድር ቢያልፉም ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ተሸንፈው በወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ።
ባለፉት ሰባት የሊጉ ጨዋታዎች ያልተሸነፉት በርንማውዞች አራቱን በማሸነፍ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።
የላውሮ ግምት፡ 1-1
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ኒውካስትል ከማንቸስተር ዩናይትድ
ኒውካስትሎች ባለፉት አራት ወራት በሜዳቸው ማሸነፍ ያልቻሉ ሲሆን ይህንንም ማሻሻል ይኖርባቸዋል።
ቡድኑ ባለፈው ሳምንት ሃደርስፊልድን በቀላሉ ያሸነፉት ማንቸስተር የናይትዶች ላይ ችግር ይፈጥራሉ ተብሎ አይጠበቅም።
የላውሮ ግምት፡ 0-2
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ሳውዝሃምፕተን ከሊቨርፑል
ቨርጂል ቫን ደይክ ወደ ቀድሞ ክለቡ ሳውዝሃምፕተን ሲመለስ የሚደረግለትን አቀባበል ማየት ያጓጓል።
ሊቨርፑሎች ጨዋታን መጨረስ ላይ ችግር ያለባቸው ሲሆን ይህም ከቶተንሃም ጋር በነበረው ጨዋታ ተስተውሏል።
የላውሮ ግምት፡ 1-1
ሰኞ
የፎቶው ባለመብት, BBC Sport
ቼልሲ ከዌስት ብሮም
ለቼልሲው አሰልጣኝ ነገሮች ጥሩ አይመስሉም። ተጫዋቾች በአሰለጣጠናቸው ደስተኛ አለመሆናቸወን የሚያሳዩ ዘገባዎችን ጋዜጦች ላይ ማየቴም አላስደሰተኝም።
ዌስትብሮሞች ከወራጅ ቀጠና ያላቸው የአራት ነጥብ ርቀት ከዚህ ጨዋታ በኋላ ይበልጥ ይጠባል ብዬ አስባለሁ።
የላውሮ ግምት፡ 2-0