የአዕምሮ መታወክን በሚያስከትሉ ህመሞች ላይ በኢትዮጵያ ጥናት እየተደረገ ነው

የፎቶው ባለመብት, BSIP
ብዙ ገንዘብ ታጠፋለች፤ በሯን ዘግታ ትቀመጣለች ፤ ከሰው በላይ የሆነች ይመስላታል፤ የእንቅልፍ ጊዜዋ በጣም አጭር ነው፤ አለባባሷ የተለየ ነው፤ ወሲባዊ ስሜቷ በጣም ከፍተኛ ደረጃ ላይ ይደርሳል፡፡
የህመሙ መጠን እየጨመረ በመጣ ቁጥር ራሷን መቆጣጠር ይሳናታል፡፡
ቅሽለቱ ቢያንስ በዓመት አንዴ ወይም ሁለቴ ይከሰትባታል።
አስፈላጊው የምክር አገልግሎትና መድኃኒት ሲሰጣት ብቻ መለስ ይልላታል።
ቤተሰብ የተስፋ ጭላንጭል አይቶ በፊታቸው ላይ የበራው ደስታ ሳይገለጥ ቅጭም ይላል፡፡
እንደገና ከፍተኛ ድብርት ይወርሳታል፡፡ ራሷን ትጠላለች ፤ ራሷን ታወግዛለች ፤ እሷነቷ ያንገሸግሻታል፡፡ እነዚህ ስሜቶቿ ከመጠን በላይ ይሆኑና ራሷን የማጥፋት ፍላጎት ላይ ያደርሳታል ።
ሌት ተቀን እርሷን መጠበቅ የቤተሰብ ሥራ ሆነ፡፡
ስሜቷን የሚያወርድ መድኃኒት ሲሰጣት ወደ ቀደመው ማንነቷ ትመለሳለች። በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ለተከታታይ ሦስት ዓመታት ሕክምናዋን ተከታተለች፡፡
በጤናዋም ላይ ቀስ በቀስ ለውጥ መታየት ጀመረ፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአዕምሮ ሕክምና ትምህርት ክፍል መምህርና ሐኪም የሆኑት ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ ካከሟቸው ሰዎች መካከል የዚችን ወጣት የጤና ጉዳይ አይረሱትም፡፡
ወጣቷ በአሁኑ ሰዓት ትዳር መሥርታ፣ ልጅ ወልዳ፣ ልጇን እያሳደገች፣ ሕይወቷን በተገቢው መልኩ እየመራች ነው።
እንደ ወጣቷ በከፋ የአዕምሮ ህመም ውስጥ አልፈው ጤንነታቸው የተመለሰላቸው ቢኖሩም ለባሰ የአዕምሮ ህመም ተዳርገው ራሳቸውን ያጠፉ እንዳሉም ፕሮፌሰር መስፍን ይናገራሉ፡፡
ለመሆኑ ቅሽለት ምንድነው?
ቅሽለት የአዕምሮ ጤና መጓደል ነው። በሕክምና ስሙ ሃይፖማኒያ (Hypomania) በመባል ይታወቃል።
መገናኛ ብዙኃን በስፋት የሚያነሷቸው የስሜት መዋዠቅ (Bipolar) እና የአስተሳሰብ መዛባት (Schizophrenia)፣ በዚሁ ቅሽለት (Hypomania) በተሰኘው የአዕምሮ ህመም ሥር የሚጠቀሱ ከባድ የአዕምሮ ጤና ችግሮች ናቸው።
አንድ ሰው ራሱን ሲያገል፣ ከሰው ጋር ለመቀላቀል ሲፈራ ፣ ትካዜ ሲያበዛ፣ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴውን ሲጠላ፣ ቤት መቀመጥ ሲጀምር፣ ለድብርት እየተጋለጠ መሆኑንና ይህም እያደገ ሲሄድ የአስተሳሰብ መዛባት (Schizophrenia) ወደተባለው የአዕምሮ ህመም እየተጠጋ መሆኑን ያመላክታል ።
ለዚህ ህመም የተጋለጡ ሰዎች ከእውነታ ጋር ያላቸው ግንኙነት የተዛባ ነው፡፡
ምክንያታዊ ያልሆነ ጥርጣሬንና ሐሳብን ሊያስቡ ይችላሉ። በስሜት ህዋሶቻቸው አማካኝነት በገሃዱ ዓለም የሌሉ ስሜቶች ሊቀበሉ ይችላሉ፡፡
ለምሳሌ ምንም ሰው በሌለበት ሁኔታ የለሆሳስ ድምጽ ሊሰሙ ይችላሉ አሊያም ዕይታ ውስጥ የሌለን ነገር ይመለከታሉ፡፡
ማኅበራዊ ሕይወታቸው ይቃወሳል። ሥራ መሥራት ይሳናቸዋል፡፡ በስሜት ወጀብ ይናጣሉ፡፡
"ወጀቡ ቅሽለት (Hypomania) የተሰኘው ህመም ላይ ይጥላቸዋል" ይላሉ ፕሮፌሰር መስፍን።
ሌላኛው የአዕምሮ ጤና እክል የስሜት መዋዠቅ (Bipolar) ነው፡፡
የስሜት መዋዠቅ የሁለት ስሜቶች መዛነፍ ውጤት ሲሆን ታማሚው ምክንያታዊ ያልሆነ ደስታ፣ ሐዘንና እንዳንዴም ከባድ ድብታን ያስተናግዳል፡፡
በዚህ ህመም የተጠቁ ሰዎች ከመሬት ተነስተው በሳቅ ሊንከተከቱ ይችላሉ አሊያም ምንም ሰበብ አስባብ በሌለበት በእንባ ይታጠባሉ፡፡
ስሜታቸው ምክንያታዊነትና ሚዛናዊነት ይጎድለዋል።
ይህ ደግሞ ለታማሚም፣ ለአስታማሚም ፣ ለሐኪምም ፈተናው ቀላል የሚባል አይደለም፡፡
እነዚህ የአዕምሮ ህመሞች ከ0.5 እስከ 1 በመቶ ሥርጭት እንዳላቸው የሚናገሩት ፕሮፌሰሩ አንደ ቀላል የሚታይ አይደለም ይላሉ።
በመሆኑም በአንድ ቤተሰብ ውስጥ እንደዚህ ዓይነት የጤና ችግር ሲያጋጥም ሌሎች የቤተሰቡ አባላት አሊያም የትዳር አጋር እገዛ ከፍተኛ መሆን እንዳለበት ይመክራሉ ።
የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ኢትዮጵያ፣ የጥናቱ መዳረሻ
በቅርቡ ለእነዚህ ከባድ የአእምሮ ህመሞች ዘላቂ መፍትሔ ለመፈለግ ያለመ ዓለም አቀፍ ሰፊ የጥናት እቅድ በኢትዮጵያ ይፋ ተደርጓል።
ዶክተር ሰለሞን ተፈራ በአዲስ አበባ የኒቨርሲቲ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ ትምህርት ክፍል ተባባሪ ፕሮፌሰር እንዲሁም በኢትዮጵያ የጥናቱ አስተባባሪ ናቸው፡፡
ጥናቱ ከባድ የአዕምሮ ህመም የሚባሉትን የአስተሳሰብ መዛባት (Schizophrenia) እንዲሁም የስሜት መዋዠቅ (Bi-polar) ላይ ትኩረት ያደረገ ነው ይላሉ፡፡
ዓላማውም የእነዚህን የጤና ችግሮች የዘር መሠረታቸውን ፣ አጋላጭ ዘሮችን (Genes) ፣ የሚከሰትባቸውን ምክንያቶችና የሕክምና ዘዴዎችን በመለየት ሕክምናውን ማፈላለግ ነው፡፡
በዚህ ዓለም አቀፋዊ ጥናት ከአፍሪካ አህጉር ኢትዮጵያን ጨምሮ ኬንያ፣ ኡጋንዳና ደቡብ አፍሪካ የጥናቱ አካል ሆነዋል፡፡
እነዚህ አገራት "ከፍተኛ የሆነ የዘር ስብጥር ያላቸው በመሆኑ፣ ልዩ ልዩ የዘር መዋቅሮችን ማግኘት ስለሚቻል እና ነባር ሕዝብ ያለባቸው በመሆኑ ለጥናቱ ጠቃሚ መረጃ ሊገኝባቸው ይችላል" ይላሉ የጥናቱ አስተባባሪ ዶክተር ሰለሞን።
ካሁን ቀደም በኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ጥናቶች የተካሄዱ ሲሆን የተወሰዱት ናሙናዎች በመቶዎች የሚቆጠሩ በመሆናቸው የአዕምሮ ጤና ችግሮቹን በስፋት ያሳዩ እንዳልነበሩ ያስታውሳሉ፡፡
"የአዕምሮ ጤና እክሎቹ ሁሉንም የሰው ዘር የሚያጠቁ በመሆናቸው በአገራት መካከል ያለው ሥርጭትም ተመሳሳይነት አለው" የሚሉት ዶክተር ሰለሞን፣ በኢትዮጵያ ከመቶ ሰዎች አንዱ ለእነዚህ የአዕምሮ ህመሞች ይጋለጣል ይላሉ፡፡
ሰማኒያ በመቶ በዘር የሚተላለፉ በመሆኑም በአገራት መካከል ያለው ሥርጭት ያን ያህል ልዩነት እንደሌለው ይናገራሉ፡፡
በመሆኑም ዓለምአቀፋዊ የሆነ መፍትሔ ለመፈለግ ኤዥያ፣ አውሮፓ፣ አውስትራሊያና ሰሜን አሜሪካም በጥናቱ ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
ከእነዚህ ክፍለ ዓለማት የተሰባሰቡ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ በዓለም ላይ የሰው ዘርን ይወክላሉ የተባሉ የዘረ መል ናሙናዎች ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ እና ኤም አይ ቲ በጋራ በሚመሩት ቤተ-ሙከራ ጥናት ይደረግባቸዋል፡፡
ይህም ከአራት እስከ አምስት ዓመታት ጊዜ ሊወስድ እንደሚችል ተገምቷል፡፡
'እኔ ከሞትኩ ሰርዶ ይብቀል'
እንደዚህ ያሉ ጥናቶችን ለማካሄድ የገንዘብ አቅም የሚጠይቁ በመሆናቸው በስፋትና በጥልቀት ለማጥናት የማይደፈር መሆኑ ተደጋግሞ ይጠቀሳል፡፡
ይህ ጥናት በአንድ በጎ ፈቃደኛ አሜሪካዊ ቢሊየነር ቴድ ሰታንሊ የኑዛዜ ገንዘብ የሚደገፍ ነው፡፡ ለጥናትና ምርምሩ ግማሽ ቢሊዮን ዶላር ሃብታቸውን ነው ተናዘው ያለፉት።
ለዚህ በጎ ተግባር ያነሳሳቸው ደግሞ ልጃቸው የስሜት መዋዠቅ (Bi-polar) ህመም ተጠቂ መሆኑ ነበር። እርሱን ለማዳን ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም፤ ይሁን እንጂ ልጃቸውን መታደግ አልቻሉም፡፡
በልጃቸው ላይ የደረሰው በሌላ ላይ አይድረስ ሲሉ "ስታንሊ ሴንተር"ን መሥርተው በአዕምሮ ጤና ችግሮች ላይ አብዝተው ይሠሩ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ እርሳቸውም ሕይወታቸው ያለፈው በቅርቡ ነው፡፡
ይህችን ዓለም ከመሰናበታቸው በፊት ግን "ዘለቄታ ያለው መድኃኒት ለእኔ ልጅ ባይደርስ እንኳን ለሌሎች ይድረስ" ሲሉ ጠቅላላ ሃብታቸውን ለዚህ በጎ ተግባር እንዲውል ተናዘዋል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚሠራው ይህ ጥናት የሚደገፈውም ቢሊየነሩ ቴድ ስታንሊ በተናዘዙት ገንዘብ መሆኑን ዶክተር ሰለሞን ጨምረው ተናግረዋል፡፡