በጃፓን "ጃቢ" አውሎ ንፋስ አስር ስው ገደለ

የፎቶው ባለመብት, EPA
አውሎ ንፋሱ ያደረሰው ጉዳት
ጃፓን ባለፉት 25 ዓመታት ታይቶ በማይታወቅ አውሎ ንፋስ ተመታለች። እስከ አሁን ቢያንስ አስር ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል። ወደ 300 ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።
"ጃቢ" የሚል ስያሜ የተሰጠው አውሎ ንፋስ በዋነኛነት ኪዮቶ እና ኦሳካ ከተሞች ውስጥ የተነሳ ሲሆን፤ የብዙዎችን ቤት ንብረት እንዳልነበረ አድርጓል።
በኦሳካ አውሮፕላን ማረፊያ የነበሩ መንገደኞች ከአካባቢው ተወስደዋል። 800 በረራዎችና የባቡር እንቅስቃሴም ተገቷል። መብራት የተቋረጠባቸው አካባቢዎችም አሉ።
አውሎ ንፋሱ ወደሀገሪቱ ደቡባዊ ክፍል እየሄደ ቢሆንም፤ የመሬት መንሸራተትና ጎርፍ ሊከሰት ስለሚችል ነዋሪዎች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል።
1.2 ሚሊየን ሰዎች የሚኖሩበት አካባቢ ለአደጋ ተጋላጭ ስለሚያደርጋቸው እንዲነሱ ተነግሯቸዋል።
በማህበራዊ ሚዲያዎች እየተሰራጩ የሚገኙ ቪድዮዎችና ፎቶዎች በአውሎ ንፋሱ ሳቢያ ህንጻዎች ተደርምሰው፤ መኪኖችም ተጨረማምተው ያሳያሉ።