አንገብጋቢ ጉዳዮች ትቶ በአለባበስ ትችት የተጠመደው የኬንያ ምክር ቤት

ተቃውሟቸውን የሚያሰሙ የኬንያ ሴቶች

የፎቶው ባለመብት, AFP

የምስሉ መግለጫ,

ተቃውሟቸውን የሚያሰሙ የኬንያ ሴቶች

በቅርቡ ይፋ የሆነው የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ የኬንያውያንን የእለት ከእለት ኑሮ አክብዶታል። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለጉዳዩ መፍትሄ ያመጣሉ ተብሎ ቢጠበቅም፤ ትኩረታቸው የነዳጅ ዋጋ ሳይሆን ሴት የህዝብ እንደራሴዎች አለባበስ ነው። ነገሩ ፍየል ወዲህ. . . የሆነበት ጋዜጠኛ ጆሴፍ ዋሩንጉ ተከታዩን ደብዳቤ ለቢቢሲ ጽፏል።

"አዘውትሬ እርቃናችንን ስለምንሸፍንበት ልብስ አስባለሁ። ይህንን ደብዳቤ ስጽፍላችሁ የለበስኩትንም ጨምሮ።

ከቀናት በፊት መኪናዬን አቁሜ ነዳጅ ስሞላ የነዳጅ ዋጋ ምን ያህል እንደናረ ሳወጣ ሳወርድ፤ በቅርቡ ነዳጅ ላይ የተጣለውን ከፍተኛ ቀረጥ በልቤ ረገምኩ።

ለዋጋ ንረቱ ተጠያቂ የማደርገው ከዓመት በፊት የተመረጡትን የህዝብ እንደራሴዎች ነው። መንግሥት ነዳጅ ላይ 16 በመቶ ቀረጥ ሊጥል መሆኑን ያውቁ ነበር። የዋጋ ጭማሪው የኬንያውያንን ኑሮ እንደሚያከብደውም አይጠፋቸውም።

ኬንያውያን ኑሮ እንዲሁም አልገፋ ብሎናል። የነዳጅ ዋጋ ጭማሪን ከድጡ ወደ ማጡ በሉት።

ታዲያ የህዝብ እንደራሴዎቻችን ስለአንገብጋቢውን የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ከመወያየት ይልቅ፤ ስለ ሴቶች አለባበስ ሲያወሩ ይደመጣሉ። ወንድ የምክር ቤቱ አባላት ስለ ሴት አባላት አለባበስ የማይሰጡት አይነት አስተያየት የለም።

የፎቶው ባለመብት, Kenya PBU

የምስሉ መግለጫ,

እጅጌ ጉርድ ልብስ መልበስ ህግ ይጻረራል ተብሏል

የምክር ቤቱ ወንድ አባላት ሴቶች እጅጌ ጉርድ ልብስ መልበሳቸው የምክር ቤቱን የአለባባስ ህግ ይጻረራል ብለው ነበር። አንዲት የምክር ቤቱ አባል ሻርፕ ለብሳ መምጣቷ የምክር ቤቱ ወንድ አባላት መነጋገሪያ ሆኖ ነበር።

የአንዲት ሴት አባል አለባበስ "ተገቢ አይደለም" በሚል ወንድ አባላት አስተያየት ሲሰነዝሩ፤ ምክትል አፈ ጉባኤው ሞሰስ ቼቦይ "እጅጌ ጉርድ ልብስ ብታደርግም ለመደበኛ ቀን የሚሆን አለባበስ ነው" ብለው አስተባብለዋል።

ኬንያውያን ስለጉዳዩ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ሲነጋገሩ ነበር። "እንዴት በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ በርካት ጉዳዮች ቸል ተብለው ስለ አለባባስ ይወራል?" ብለው ይጠይቁም ነበር።

የነዳጅ ዋጋ መጨመር ብቻ ሳይሆን፤ ድህነት፣ የመሰረተ ልማት ውስንነትም ሀገሪቱን እየፈተኗት ነው። እነዚህ ጉዳዮች ግን ቸል ተብለዋል።

በአንድ ወቅት ልጆቻቸው ለዴሞክራሲ መከበር ሲታገሉ የታሰሩባቸው እናቶች እርቃናቸውን ሰላማዊ ሰልፍ አድርገው ነበር።

የኖቤል የሰላም ተሸላሚ ዋንጌሪ ማታይን ጨምሮ በኬንያ መዲና ናይሮቢ የተገኙ ሴቶች መንግሥት ለጥያቄያቸው መልስ እንዲሰጥ መለመላቸውን አደባባይ በመውጣት አስገድደዋል።

የኬንያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሴቶች አለባባስ ላይ ያሳዩት ያልተገባ ጣልቃ ገብነት እየተተቸ ነው። "ማይ ድረስ ማይ ቾይስ" [አለባበሴ ምርጫዬ] የተባለ ንቅናቄ የተጀመረውም ለዚህ ነው።

በዓለም ላይ ያሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤቶች ውስጥ ድብድብ፣ የስድብ ልውውጥ፣ ሴቶችን ማጥላላትም ታይቷል። በኬንያ ምክር ቤትም እንዲሁ።

የምክር ቤቱ አባላት ስንመርጣቸው የሰጠናቸውን ኃላፊነት መወጣት አለባቸው። በሴት አባላት የአለባበስ ምርጫ ጣልቃ ከመግባትም ይቆጠቡ።"

ጋዜጠኛው የምክር ቤቱ አባላት ቀልባቸውን ሰብሰብ አድርገው ለሀገሪቱ ችግር መፍትሄ እንዱሰጡ ይጠይቃል። በሴቶች የልብስ ምርጫ ጣልቃ መግባት ተገቢ አለመሆኑንም ያስረጋጣል። ለቢቢሲ የጻፈው ደብዳቤ "ሌተርስ ፍሮም አፍሪካን ጆርናሊስትስ" (ከአፍሪካውያን ጋዜጠኞች የተላኩ ደብዳቤዎች) በተሰኘ ገጽ ላይ ተስተናግዷል።